ወጥቶ የቀረው ኢትዮጵያዊው የጥበብ ሊቅ- ገብረክርስቶስ ደስታ


ለዛሬ ይዤላችሁ የቀረብኩት ኢትዮጵያዊ ጥበበኛ፣ ኢትዮጵያን እጅግ የሚወዳት፣ በኢትዮጵያ የሥዕል እና የሥነ-ግጥም ዓለም ውስጥ ድምቅምቅ ብሎ ሁሌም ስሙ ስለሚጠራው ስለ ታላቁ ጥበበኛችን ስለ ገብረክርስቶስ ደስታ ነው። ገብረ ክርስቶስ ደስታ “ስሞት ሀገሬ ቅበሩኝ” እያለ በግጥም እየተቀኘ ሲማፀን የኖረ ባለቅኔ ቢሆንም፤ ሞቶ የተቀበረው ግን በባዕድ ሀገር ነው።
ገብሬ “ሀገሬ” ብሎ ሲቀኝ እንዲህ አለ፡-
ውበት ነው አገሬ
ገነት ነው አገሬ
ብሞት እሄዳለሁ ከመሬት ብገባ
እዚያ ነው አፈሩ የማማ ያባባ
ባሳብ እሄዳለሁ ቢሰበርም እግሬ
አለብኝ ቀጠሮ ከትውልድ አገሬ።
አለብኝ ቀጠሮ
ከትውልድ አገሬ ካሳደገኝ ጓሮ
“ብሞት እሔዳለሁ ከመሬት ብገባ” እያለ የዛሬ 50 ዓመት ግጥም የፃፈ ሰው ዛሬም አፅሙ በምድረ አሜሪካ ነው። ዛሬ ስለ ጥበበኛው ገብረክርስቶስ ደስታ ጥቂት ነጥቦችን እንጨዋወታለን።
ገብረክርስቶስ ደስታ ጥቅምት 5 ቀን 1924 ዓ.ም በሐረር ከተማ አደሬ ጢቆ ተወለደ። አባቱ አለቃ ደስታ ነግዎ ሲባሉ እናቱ ደግሞ ወ/ሮ አፀደማርያም ወንድማገኝ ይባላሉ።
ገብረክርስቶስ ደስታ በ1920ዎቹ ወደዚህች ዓለም ብቅ እንዳሉት የኢትዮጵያ ብርቅዬ ልጆች መካከል አንዱ ነው። የሥዕል ጥበብ ገና ሕፃን ሳለ ጀምሮ ውስጡ ተፀነሰ። ገና የአስር ዓመት ልጅ ሳለ ሐረር ውስጥ ተወዳጅ ሥዕሎችን መውለድ የቻለ የጥበብ ክስተት ነበር።
እንዲህ እያለ የሥዕል ጥበብ ውስጡ እየዳበረ መጣ። ከዚያም ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ሳይንስ ፋክሊቲ ገባ። ለሁለት ዓመታት ተምሮ አቋረጠ። ቀጥሎም ወደ ጀርመን ሀገር ሔዶ በኮሌኝ የሥዕል አካዳሚ ተማረ። ወደ ሀገሩ ኢትዮጵያም መጥቶ ማስተማር ጀመረ። በ1955 ዓ.ም የሥዕል አውደ-ርዕይ ሲከፍት በሥራዎቹ ተደንቀው መጥተው የከፈቱለት እና የመረቁለት ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ነበሩ። ከዚያም በ1958 ዓ.ም በሥዕል ጥበብ የቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ ሽልማት ድርጅት የሸለመው የኢትዮጵያ ብርቅዬ አርቲስት ነው እየተባለ ብዙ ተፅፎለታል።
ኢትዮጵያ ውስጥ በአንድ ሰው ሕይወት እና ሥራዎች ዙሪያ ሰፊ ውይይትና ክርክር ከተደረገባቸው ሰዎች መካከል እንደ ገብረክርስቶስ ደስታ ትልቁን ድርሻ የሚወስድ የለም። ገብረክርስቶስ ደስታ ሕይወቱና ሥራዎቹ እየተተነተኑ የቀረቡበት አጋጣሚው በራሱ ሊነገርለት ስለሚገባ እሱንም ላውጋችሁ።
ገብሬ በዘመነ ደርግ ከሥርዓቱ ጋር ችግር ስለተፈጠረበት ወደ ኬኒያ ተሰደደ። ከዚያም ወደ ጀርመን ሐገር ሄደ። ጀርመን ሀገር ውስጥ በርካታ የሥዕል ሥራዎቹን ተአምር ሊባል በሚችል መልኩ ሠራ። አያሌ የጀርመንና የአውሮፓ ሠዓሊያን ጥበበኞች በዝህ ሰው ሥራዎች በእጅጉ ይደነቁ ነበር። ገብረክርስቶስ ስለ ሥዕል ጥበብና በአጠቃላይ ስለ ኪነ-ጥበብ ሲናገርና ሲያቀርብ ለመስማት ለማየት ልሂቃን ከያሉበት ይሰባሰቡ ነበር። ከኢትዮጵያ ምድር የተከሰተ የጥበበኞች አውራ ሆኖ አውሮፓ ውስጥ ተከሠተ። ሰፊ መነጋገሪያም ሆነ።
ግን ደግሞ፤ ሐገሩ ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ ዜጐች በፖለቱካ ልዩነቶቻቸው እየተገዳደሉ፣ የበርካታ እናቶችና አባቶች ለቅሶና ጩኸት እየተሰማው ሠላም እንዳጣ ይነገራል። ጥንታዊቷ ኢትዮጵያ ውስጥ የዜጐቿ ፍጅት እና እስራት፣ ቶርቸር ጥበበኛው ገብሬ ጀርመን ውስጥ ቢኖርም ጉዳዩ ይበጠብጠው ጀመር። እና አሁንም መራቅ መሄድ ፈለገ። ደሞ ወደ ዓለም ጥግ። ከጀርመን ብርር ብሎ ሊሄድ ተነሳ። አንድ ነገር ደግሞ አሰረው። በርካታ የሚባሉ፣ ዓለም በቅርስነት እንደ ዓይኑ ብሌን የሚያያቸውን ሥዕሎች ሠርቷል። እነሱን ምን ያድርጋቸው? ልጆቹ ናቸው።
ኸረ ልጅ ማሰሪያው ኸረ ልጅ ገመዱ
ጐጆማ ምን አላት ጥለዋት ቢሔዱ
ይላል የሐገሬ ሰው። እናም ገብሬን እነዚህ የጥበብ ልጆቹ ያዙት። ከራሱ ጋር ሲሟገት ቆየ እና አንድ መላ ዘየደ።
ጀርመን ያደገ የበለፀገ ምድር ነው። ለጥበብና ለጥበበኛ ከፍተኛ ክብር ያለው ሥርዓት ነው። ስለዚህ ገብሬ ለጀርመን መንግስት ተናዘዘ። ኑዛዜው እንዲህ ይላል፡-
“ውድ የጀርመን መንግስትና ሕዝብ ሆይ፤ ሀገሬ ኢትዮጵያ ሰላም ሆና የተረጋጋች ወቅት እነዚህን ሥራዎቼን ወደ ሀገሬ ላኩልኝ እስከዛው ከናንተ ዘንድ ይኑርልኝ። አደራ” ይላል።
ይህ ኢትዮጵያዊ የጥበብ ባለቅኔ ይህን ከተናዘዘ በኋላ
ውበት ነው አገሬ
ገነት ነው አገሬ
ብሞት እሄዳለሁ ከመሬት ብገባ
እዚያ ነው አፈሩ የማማ ያባባ
እያሉ የኢትዮጵያን ፍቅሩን ራሮቱን የተነፈሰበትን ታላቁን ግጥም ፃፈ። ግን ደግሞ እንደገና ተሰደደ። ከጀርመን ወደ አሜሪካ ሄደ።
ታላቁ ደራሲ በዓሉ ግርማ፣ እውነተኛ ደራሲ ነብይ ነው ይል ነበር። እናም ገብረክርስቶስ ደስታ ምድር ላይ ብዙም እንደማይኖር የተረዳ ይመስላል። ምክንያቱም ለጀርመን መንግስትና ሕዝብ ተናዘዘ። ሀገሬ ብሎ ግጥም ፅፎ ብሞትም ሀገሬ እሄዳለሁ እያለ ተቀኘ። ወዲያውም ወደ አሜሪካ ሄደና ሎውተን ኦክላሆማ ውስጥ ለትንሽ ግዜ ሥዕል ሲያስተምር ቆይቶ መጋቢት 21 ቀን 1974 ዓ.ም የኢትዮጵያ የጥበብ ፈርጥ የሆነው ታላቁ ባለቅኔ በድንገተኛ ህመም ብቻውን ሆስፒታል ገብቶ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ማየት እንደናፈቀ ማረፉ ተነገረ። ሥርዓቱ ቀብሩም እዚያ ተፈፀመ። ኢትዮጵያ እስከ ዛሬ ድረስ የዚህን የጥበበኞች ሁሉ አውራ የሆነውን የዜጋዋን አፅም ወደ ትውልድ ቦታው አምጥታ በሥርዓት ሐውልት አላቆመችለትም።
ግን ደግሞ በ1995 ዓ.ም እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ ያለው የጀርመን የባህል ተቋም /ጐተ-ኢኒስቲቲዩት/ የፕሮግራም ክፍል ኃላፊ የሆኑት ወ/ሮ ተናኘ ታደሰ ከባልደረቦቻቸው እና ከገብረክርስቶስ ደስታ ጓደኞች፣ ተማሪዎች እና ወዳጆች ጋር በመሆን የዚህን ሰው ኑዛዜ ለማስፈፀም እንቅስቃሴ አስጀመሩ። “ሀገሬ ሰላም ከሆነች ሥዕሎቼን ወደ ሀገሬ ውሰዱልኝ” ያለውን ኑዛዜ ለማስፈፀም ሰፊ ዘመቻ ተጀመረ።
ከዘመቻው ውስጥ አንዱ ገብረክርስቶስ ደስታ ማን ነው? ምን አይነት ኢትዮጵያዊ ነው? ለሀገሩና ለዓለም ሕዝብ ያበረከተው አስተዋፅኦ ምንድን ነው? ሥራዎቹ እንዴት ይታያሉ? እንዴትስ ይተነተናሉ? የገብረ-ክርስቶስን ታላቅነት ጥበበኛነት ትውልድ ሁሉ እንዲማርበት፣ ዘላለማዊ እንዲሆን ምን ይደረግ ተብሎ እነ ወ/ሮ ተናኘ ታደሰ አቀዱ፣ እቅዳቸውንም ለማስፈፀም ሥራ ተጀመረ።
የመጀመሪያው ውይይት 1995 ዓ.ም አራት ኪሎ በሚገኘው የጀርመን የባህል ተቋም ውስጥ ተደረገ። የውይይቱን መነሻ ሀሳብ እንዲያቀርቡ የተጋበዙት የገብሬ የልጅነት ጓደኛ ተባባሪ ፕሮፌሰር ተስፋዬ ገሠሠ እና የገብሬ የሥዕል ተማሪ የነበረው ዮሐንስ ገዳሙ ናቸው። በውይይቱም አያሌ ታዳሚያን ቢገኙም ረብሻ ተነሳ። የረብሻው መነሻ ተስፋዬ ገሠሠ ገብረክርስቶስ ደስታ በአንድ ወቅት ስላጋጠመው የቆዳ ህመም /ለምፅ/ ደጋግመው ሲናገሩ፣ አቁም! ይሄን አትናገር! ስለ ሥራውና አበርክቶው አውራ የሚል እንደ ብራቅ የጮኸ ድምፅ መጣ። ለተወሰኑ ደቂቃዎች ውይይቱ ታወከ። ከዚያም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አንጋፋው የሥነ-ጽሑፍ ምሁር ዶ/ር ፈቃደ አዘዘ አረጋግተውት ውይይቱ እንደገና ተጀመረ። እንደገና ሲጀመር ተስፋዬ ገሠሠ ስለ ገብሬ አፍነው ያቆዩአቸውን እርሳቸው ምስጢር ናቸው ብለው የሚያምኑባቸውን ድብቅ ታሪኮች በይፋ ተናገሩ። ግን የህዝቡ ስሜት አሁንም የዚህን ጥበበኛ ታሪክ የበለጠ ማወቅ ነበር። ሌላ ቀጠሮ ተያዘ።
በሁለተኛው ቀጠሮ ላይ ስለ ገብረክርስቶስ ደስታ የግጥም ሥራዎች ትንታኔ ይዘው የመጡት ዶ/ር ፈቃደ አዘዘ ነበር። አዳራሹ ከአፍ እስከ ገደፉ ሞላ። ዶ/ር ፈቃደ ገብረክርስቶስ ደስታ ምን አይነት ባለቅኔ እንደነበር እየዘረዘሩ አቀረቡ። ግጥሞቹን ሲያነቧቸውም የህዝቡ ስሜት ከፍተኛ ነበር።
ከዚያም ውይይት ተጀመረ። በውይይቱ መሀል አንድ ጥያቄ ተነሳ። ገብረክርስቶስ ደስታ ሠዓሊ ነው ወይስ ገጣሚ የሚል። አደገኛ ክርክር ተፈጠረ። ሠዓሊዎቹ ገብሬ ሠዓሊ ነው፤ ገጣሚነቱ ከሥዕል ቀጥሎ ነው የሚመጣው አሉ። የሥነ-ፅሁፍ ሠዎች ደግሞ ኸረ ሰውዬው ታላቅ ባለቅኔ ነው እያሉ የማይቋጭ ማብራሪያ ሰጡ። ክርክሩ መቋጫ አጣ። መሸ። እንደገና ሌላ ቀጠሮ ተያዘ። ገብሬ ሠዓሊ ነው ገጣሚ በሚለው ለመከራከር የዩኒቨርሲቲ ምሁራን፣ ጋዜጠኞች፣ ጥበበኞች ቀጠሮ ያዙ።
በቀጠሮው ቀን ዶ/ር ፈቃደ አዘዘ አወያይ ሆኑ። ቀኑ የአዋቂዎች የጦርነት ቀን ይመስል ነበር። በዕውቀት አደባባይ የሚደረግ ፍልሚያ ነበር። ሠዓሊዎች ሽንጣቸውን ገትረው ገብሬ ምን ያህል የሥዕል ጥበበኛ እንደነበር ማስረጃቸውን ይዘው መጡ። ሠዓሊ እሸቱ ጥሩነህ እና ቀራፄ በቀለ መኮንን እና ፕ/ር አቻምየለህ ደበላ ከአሜሪካ ድረስ መጥተው የገብረክርስቶስን ሠዓሊነት ሲተነትኑ አመሹ።
ይሄ ሳይቋጭ ገብሬ አዝማሪ ነው፤ የሙዚቃ ሰው ነው እያለ ግጥሞቹን ከሙዚቃ አንፃር የሚተነትን መጣ። እሱም ዛሬ በህይወት የሌለው የሥነ-ግጥም መምህሩ ብርሃኑ ገበየሁ ነበር። የብርሃኑ ገበየሁ ገለፃ እንደ ተአምር ሲደመጥ ከቆየ በኋላ ሌላ አስገራሚ ነገር ብቅ አለ።
የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የሆነው ገጣሚ ነብይ መኮንን ደግሞ ገብሬ እናንተ እንደምትሉት ብቻ አይደለም። ገብሬ የሳይንስ ሰው ነው ሲል ገለፀው። ሲያብራራውም ሥዕሎቹም ሆኑ ግጥሞቹ የሳይንስ ፅንሠ ሃሳብ በከፍተኛ ደረጃ የሚያንፀባርቁ ናቸው እያለ ተነተነ።
ውይይቱ መቋጫ አጣ። ገብሬ ይሄ ነው ተብሎ መደምደምያ ጠፋለት።
በመጨረሻም ታላቁ የሥነ-ፅሁፉ ምሁር ዶ/ር ዮናስ አድማሱ፣ አንድ ማሳረጊያ አቀረቡ። ማናችሁም ብትሆኑ ይሄን ሰው መግለፅ አትችሉም። ይህ ሰው በሁሉም መስክ ጥበበኛ ነው። ስለዚህ ሠዓሊ፣ ገጣሚ፣ አዝማሪ፣ የሳይንስ ሰው፣ ብትሉት በቂ አይደለም። እንዲህ ዓይነት ሰው ከያኒ ነው የሚባለው በማለት መቋጫ ያልተገኘለትን ክርክር ፈር አስያዙት።
ውይይቱ እንዲህ እያለ ለብዙ ጊዜ ከሄደ በኋላ ገብሬ የብዙ ሰው ቀልብ ገዛ። ከዚያም በኑዛዜው መሠረት ሥራዎቹ ወደ ሀገሩ ኢትዮጵያ እንዲመጡ ጉትጐታ ተጀመረ። የጀርመን መንግስትም ተባበረ። እዚህ አዲስ አበባ ውስጥም የገብረክርስቶስ ደስታ ማዕከል በሚል አ.አ.ዩ ቤት ሰጠ። በስሙ ጋለሪ ተከፈተ። እናም በመጨረሻ እነዚያ የሰው ልጅ ሁሉ ቅርስ የሆኑት ሥዕሎቹ ከጀርመን ወደ ሀገሩ ኢትዮጵያ መጥተው ዛሬ እዚህ 6 ኪሎ ይገኛሉ። እነዚህን ተአምራዊ ሥዕሎቹን ሁላችሁም ሄዳችሁ ጐብኟቸው። እነሱን ስታዩ ኢትዮጵያ ምን አይነት የጥበበኞች ሁሉ አውራ የሆነ ሊቅ እንደነበራት ትረዳላችሁ።


Comments

Popular posts from this blog

ኢትዮጵያዊው የታሪክ ፍቅረኛ