ኢትዮጵያዊው የታሪክ ፍቅረኛ






ለዛሬ ይዤላችሁ የቀረብኩት ኢትዮጵያዊ ወግና ቁም ነገር ሁሌም ባወራለት ስለማይሰለቸኝ ሰው ነው።
ኢትዮጵያ የታላላቅ ታሪኮች ባለቤት መሆኗን፣ የሰው ዘር መፈጠሪያ እንደሆነች ለመጀመሪያ ጊዜ ስላበሰረውና እንዲሁም ደግሞ በኢትዮጵያ ፍቅር ወድቆ ዜማውም፣ ብዕሩም፣ ቴአትሩም፣ ግጥሙም፣ መንፈሱም ኢትዮጵያ እንደሆነች በፍቅር ስለተለያት ባለቅኔው ሎሬት ፀጋዬ /መድህን ይሆናል፡-

ኢትዮጵያ እና ሕዝቦችዋ በመድረክ ላይ ገዝፈው እንዲወጡ፣ በታሪክ ውስጥ ገናና ህዝቦች እንደሆነ ሲፅፍላቸው፣ የኢትዮጵያም አንድነት ከብረት በደደረ መልኩ እንዲጠነክር ለኢትዮጵያ ሰማዕት የሆኑ ባለታሪኮችን በምሳሌነት እያቀረበ ፀጋዬ /መድህንት ብዙ የሰራ የዚህች ሀገር ባለቅኔ ነው።

ፀጋዬ አፄ ቴዎድሮስ መቅደላ ላይ ሽጉጣቸውን መዝዘው ራሳቸውን ለኢትዮጵያ ሲሉ የሰውበትን ታሪክ በመመርኮዝ የንጉሡን ስብዕና ወደ ፍልስፍና ቀይሮታል። ይህም ፍልስፍና ቴዎድሮሳዊነት እንዲባል ያደረገበት ነው። ቴዎድሮሳዊነት ማለት ለሐገር ክብር፣ ለኢትዮጵያ ፍቅር ራስን መሰዋትን ይመለከታል። ፀጋዬ ቴዎድሮስ በተሰኘው ግዙፍ ቴአትሩ ያሳየው ይህን ፍልስፍና ነው። ከኢትዮጵያ በላይ ምንም ነገረ የለም በማለት ራስን መስጠት። የኢትዮጵያን ክፉ ከማይ እኔ በቅድሚያ ልሰዋ ማለትን በቴዎድሮስ በኩል አሳይቷል።

አፄ ቴዎድሮስ ይህችን ኢትዮጵያ ብለን የምንጠራትን ሐገር አንድነቷ ተጠብቆ፣ አንዲት ታላቅ ሀገር የመመስረት ህልም እና ይሄን ህልም ዕውን ለማድረግ የወጡ የወረዱበትን የትግል ሜዳ በማሳየት ታላቅ ህልም እንደገና ሊጨልም አፋፍ ላይ ሲደርስ እና ተስፋ ሲያስቆርጥ የኢትዮጵያን ክፉ ከማይ ልሰዋ ያሉበትን ታሪክ በመምዘዝ ኢትዮጵያዊነትን ያስተማረበት ትልቅ ቴአትሩ ነው።
በዚህ ተውኔት ሁሉንም ታዳሚ በመንፈስ በማሳተፍ ኢትዮጵያዊነትን ከፍ ያደርጋል። አፄ ቴዎድሮስም እንዲህ ይላሉ።

ለማናችንም ቢሆን ከእንግዲህ ከቶ እረፍት የሚሉት የለም። ሁሉም ፋንታውን ይጣር! ይድከም! በአዲስ መንፈስ ይነሣ!... ዛሬ በኢትዮጵያ የመከራ ቀን ይኸው ያለሕያው እግዚአብሔር ወገን የላትምና፣ ዛሬ በኢትዮጵያ በነፃነቷ በታሪኳና በሕዝብዋ አንድነት የመከራ ቀን፣ ያልተነሳላሰትን፣ ያልታጠቀላትን የሀገር ወገን፣ እኔ አባ ታጠቅ በስመ ቃሉ ረግጬዋለሁ! ይኸው እርግማኔ ይድረሰው! በዚህች በመከራዋ ሰዓት ላላቀፉት፣ ላልቀሙላት ወገን ከቶም ዘር አይቁምላት። ያልደገፉት ደጋፊ ይጣ! ብድሯን ያልከፈለ ልጅ ዕዳው በልጅ ልጆቹ ግፍ ይክፈለው። የኢትዮጵያ ሐቋን የከለከላት ሐቁ ስላቅ ሆኖ ይነቀው። እትብቷን የገፈፈ የገዛ እትብቱ እባብ ሆኖ ይጥለፈውይኸው ለማናችንም ቢሆን የኢትዮጵያ ልጅ ነኝ፣ ወገን ነኝ ለሚል ወገን ከእንግዲህ ከቶም እረፍት የሚሉ የለም።

ይሄ ሁሉ የአፄ ቴዎድሮስ እርግማን የሚዘንበው የእንግሊዝ ወታደሮች የኢትዮጵያን ድንበር ደፍረው በመግባታቸው ይህንን ድፍረት ለመከላከል ወደ መቅደላ ላልመጡ፣ የሀገራችን ጥቃት ላልተከላከሉ ሰዎች የቀረበ እርግማን ነው።

የኢትዮጵያ ግዙፍነት፣ ኢትዮጵያ ማለት ፍቅር ማለት እንደሆነችና ይህንንም ፍቅሯን ታላቅነቷን ማጣት ደግሞ የማይገባ መሆኑን ፀጋዬ በቴዎድሮስ ውስጥ ገብቶ ያሳያል።
ሎሬት ፀጋዬ በቴዎድሮስ ብቻም አያልቅም። ኢትዮጵያዊነትን ለመገንባት ሌሎች ታላላቅ ሰብዕናዎችንም ይጠቀማል። ለምሳሌ አቡነ ጴጥሮስን እንደ ገፀ-ባህሪ ወስዷቸው እርሳቸውንም ወደ ፍልስፍና ቀይሯቸዋል። ፍልስፍና ጴጥሮሳዊነት ይባላል። ጴጥሮሳዊነት የሃይማኖት ሰው ሆኖ ውሸት ቅጥፈት፣ በደል፣ መከራ፣ ግድያ ሲፈፀም ዝም ብሎ አለማየት ነው። ጴጥሮሳዊነት የሃይማኖት ሰው ሆኖ ለኢትዮጵያ መሞትን፣ ለኢትዮጵያ ሲባል በጥይት ተደብድቦ መገደልን የሚያሳይ ጥልቅ ፍልስፍና አድርጎት ሎሬት ፀጋዬ /መድህን ወደ መድረክ አመጣው።

ፀጋዬ /መድህን ጴጥሮስ ያቺን ሰዓት በተሰኘው ቴአትሩ በተሰኘው ቴአትሩ አቡነ ጴጥሮስ የኢጣሊያ ፋሽስቶች ኢትዮጵያን ወርረው፣ ሕዝቡን ሲያሰቃዩ፣ ሀገሪቷን በቅኝ ለመግዛት ሲዶልቱ እምቢኝ አሻፈረኝ ብለው ፋሽስቶችን በግላጭ ሲያወግዙ ታስረው ተሰቃይተው፣ ከእርስም እንዲለቀቁ ፋሺስቶች የኢትዮጵያን ህዝብ ስበኩልን ብለዋቸው ሁሉ ጠይቀዋል። ግን አቡነ ጴጥሮስ ለኢጣሊያ ፋሽስቶች የተገዛ ኢትዮጵያዊን ገዘቱ። እናም ደረታቸውን ለመትረየስ ጥይት ሰጥተው ለኢትዮጵያ ክብር ሲሉ እስከ ወዲያኛው አሸለቡ። ጴጥሮሳዊት ይህ ነው። ለኢትዮጵያ መሞት።

በጣም የሚገርመው ነገር አቡነ ጴጥሮስ ፋሽስቶችን ሲቃወሙ፣ በተቃራኒው ደግሞ ለፋሽስቶች ያደሩ የሃይማኖት አባቶች ነበሩ። ጴጥሮሳዊነት ልዩነት የሚያመጣው በዚህ ወቅት ነው። ለእውነት፣ ለሀገር መሰዋትን። ፀጋዬ /መድህን በነዚህ ታላላቅ ሰዎች ታሪክ ውስጥ ኢትዮጵያዊነትን የሚገነባ የብዕር አርክቴክት ነበር።

ሎሬት ፀጋዬ መች በነዚህ ብቻ ያቆማል። ዘርአይ ደረሰ በሮም አደባባይ ለኢትዮጵያ ክብር ሲል የዋለውን ውለታ ቴአትር ጽፎለት ወደ መድረክ አምጥቶ ኢትዮጵያዊነትን አስተምሮበታል። የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ተደፈረ ብሎ ዘርአይ ደረስ የከፈለውን መስዋዕትነት ጎልቶ እንዲታይ ያደረገ የጥበባት ሊቅ ፀጋዬ /መድህን ሁሌም ስሙ ይነሳል።
ፀጋዬ ጉዳዩ አያልቅም። የኢትዮጵያዊነትን መሠረትና ካብ እያነፀ በህዝቦች ውስጥ ትልቅ አምድ ያስቀመጠ ነው። ሌላው ግዙፍ ቴአትሩ ምኒልክ የሚሰኘው ነው። በአፄ ምኒልክ አመራርና ጀግንነት ውስጥ ኢትዮጵያዊነትን አስተምሯል።

ፀጋዬ / መድህን ምኒልክ በተሰኘው ታሪካዊ ተውኔቱ ላይ በምኒልክ አንደበት እንዲህ ይላል፡-

ሰው በተለይም የመንግስት ኃላፊነት ያለው ሰው ባለው ነገር ላይ እንጂ በተጨባጭ በሚዳሰሰውና በሚጨብጠው ነገር ላይ እንጂ፣ በሚመኘውና በሚያልመው የሃሳብ እስትንፋስ ላይ ዓላማውን ሊያዋቅርና ሊገነባው አይችልም። ለዚህ ነው ያገርህን ያበሻን ቤት አሰራር ተጨባጭ አገነባብ ባጭር ምሳሌ ላስተምርህ ማለቴአየህ ኢያሱያበሻ ቤቱ፣ ያበሻ፣ ጣሪያው ምሶሶ ጉልላቱ፣ ያበሻ ማዕዱ ምድጃና መሶቡ ያበሻ አውድማው አዳራሹና አደባባዩ እንደ ፀሐይ ኮከብ ብርሃን ጮራ፣ እንደ ቀለበት የህብር ዙሪያ እንደ ክበብ ነው። ባህልህን አስጠንቅረህ ካላወክ አገርህም አያውቅህ! ሕዝብህም አታውቀው! ሕዝብህን ማወቅ ማለት የሕዝብህን የባህል ብልት ጠንቅቀህ መገንዘብ ነው። ሕዝብህን ማወቅ ደግሞ አገርህን ማወቅ ነው። ማንነቱን ያላጤንክለትን ህዝብ ነገ ማስተዳደሩ ያቅትሃል እያሱ….

ይላሉ አጤ ምኒልክ የልጅ ልጃቸውን ወራሴ መንግስታቸውን ሲመክሩት። ይህን ምክር ፀጋዬ /መድህን ምኒልክ በተሰኘው ግዙፍ ቴአትሩ ውስጥ ፅፎታል።

ፀጋዬ /መድህን እነዚህን ታላላቅ ኢትዮጵያዊያንን በመድረክ ላይ ነብስ ዘርቶባቸው እያናገራቸው ስለ ኢትዮጵያዊነት እና ስለ ኢትዮጵያ የረጅም ዘመን ታሪክ ሲገነባ የኖረ የብዕር ሰው ነበር።

ፀሐፌ- ተውኔት ፀጋዬ /መድህን ቅኔዎችም ሆኑ የተውኔት ፅሁፎች፣ በሁሉም ሀገር ቋንቋዎች ታትመው የሀገር ባህል አስተዋውቀዋል። ፕሬዘንስ አፍሪካን፣ አፍሪካን ፐየትስ፣ አንቶሎጂ፣ ሎተስ፣ ወዘተ ባሉት አለም አቀፍና የአፍሪካ ታላላቅ የሥነ-ፅሁፍ መድብሎች ውስጥ ታትመዋል። በእንግሊዝኛ የፃፋቸው ታሪካዊ ተውኔቶቹ በአፍሪካ የተለያዩ ቦታዎችና በአውሮፓም እንደ ለንደን፣ ሮም፣ ኮፐንሀገንና ቡዳሬስት ባሉ ከተሞች፣ በአሜሪካም በኮሎምቢያም ዋሽንግተን ካሊፎርኒያ እና በሚኒያፖሊስ ዩኒቨርስቲዎች በመድረክ ታይተውለታል። ኮልዡን ኦፍ አልታርስ፣ ቴዎድሮስ…. ዳካር ሴኔጋል ድረስ ተጠርቶ ከተሸለመው ኮማንደር ኦፍ ሴኔጋል ናሽናል ኮን ኒሻን ሽልማት ጀምሮ ሌሎች አለም አቀፍ ክብርና ሽልማቶችን ያገኘ የዚህች ሀገር ብርቅ ሰው ነበር።

Comments

Post a Comment

Popular posts from this blog

ወጥቶ የቀረው ኢትዮጵያዊው የጥበብ ሊቅ- ገብረክርስቶስ ደስታ